(መሠረት ሚድያ)- የኢፌዲሪ ስራና ክህሎት ሚንስቴር በቅርቡ የውጭ ሀገር ስራ ስምሪት አዋጅ ቁጥር 923/2008 እና ማሻሻያውን አዋጅ ቁጥር 1246/2013ን የሚተካ አዲስ አዋጅ ለማውጣት እየተንቀሳቀሰ እንደሆነ ይታወቃል፡፡
ለዚህም ሲባል ሁለት ጊዜ ኤጀንሲዎችን ሚንስቴር መ/ቤቱ ለስብሰባ የጠራ ሲሆን በሁለቱም ስብሰባዎች ላይ ተነግሯል፡፡
ነገር ግን እንደ ሀገር ባሁኑ ሰአት ከገጠሙን ችግሮች ውስጥ አዋጆችን በጥናት ላይ ተመስርቶ፣ ሀገራዊ ራእይ እና የረጅም ጊዜ ተቋማዊ እቅድ ይዞ ከማፅደቅ ይልቅ፣ ሚንስትሮች በተቀያየሩ ቁጥር ለራሳቸው የሚመቻቸውን የፈለጉትን ለመጥቀም ያልፈለጉትን ለመጉዳት የሚመስሉ አዋጆች ሲወጡ ይታያል፡፡
ከዚያም አፍታ ሳይቆይ ሌላ ባለስልጣን ሲመጣ አዲስ አዋጅ ለማውጣት ሲንቀሳቀስ ማየት የተለመደ እየሆነ መጥቷል፡፡ ለዚህም እንደማሳያ በቅርቡ በረቂቅ ደረጃ ላይ የሚገኘው እና በ2013 ሰኔ ወር መጨረሻ ማሻሻያ ተደርጎበት በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ፀድቆ በስራ ላይ ይገኝ የነበው አዋጅ ቁጥር 1246/2013 ነው፡፡
ይህ አዋጅ በተሻሻለ አራት አመት እንኳን ሳይሞላ፣ እንዲሁም በቂ ጥናትና ዝግጅት፣ ብሎም የባለድርሻ አካላት በቂ የሆነ አስተያየት ሳይታከልበት ለማፀደቅ እየተሮጠ ሲሆን በያዛቸው አንቀጾች ምክንያት ከአመታት በኋላ ይሻሻልን በድጋሚ የተወካዮች ም/ቤቱ ድጋሚ ሊጠየቅ እንደሚችል ከወዲሁ ግምታችንን ማስቀመጥ እንችላለን፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ም/ቤቱም ለምን እንደዚህ እየሆነ እንዳለ የማይጠይቅበት ምክንያት ግራ የሚያጋባ ነው፡፡
ከኤጀንሲዎች ማህበራትና ፌዴሬሽን የአዋጁን ረቂቅ ስጡንና በኛ በኩል አለን የምንለውን ግብአት በዝርዝር በደብዳቤ እንስጣቹ ተብሎ የተጠየቀው መ/ቤቱ ግን አንድ ጊዜ የማህበር ሀላፊዎችን በመጥራት በንባብ ያወያየ ሲሆን በሁለተኛው ደግሞ የኤጀንሲ ባለቤቶችን ሁሉ ጠርቶ በፕሮጀክተር ማስፈፀም የፈለገውን ነገር ተናግሮ ወርዷል፡፡
ከዚያ ውጭ ግን አስተያየት ለመቀበል ፍቃደኛ አለመሆኑን በንግግርም ባይሆን በተግባር ገልፀውልናል፡፡ በውይይቱ ላይ አዋጁ ስለያዛቸው አንቀጾች በተነገረበት ወቅት ከዚህ በፊት በተግባር ተሞክሮ ያልተሳካ አሰራርም በአዋጅ ለማስደገፍ እየተሞከረ እንደሆነ ለመረዳት ችለናል፡፡
ይኸውም ስራ ፈላጊ ዜጎችን እራሱ ሚንስቴር መ/ቤቱ መዝግቦ ለኤጅንሲዎች በኮታ የሚሰጥ ሲሆን ከዚህ ውጭ ማንኛውም ሰው በፈለገው ኤጀንሲ ሙሉ በሙሉ መጠቀም የተከለከለ መሆኑን በረቂቁ ላይ መቀመጡን ለመገንዘብ ችለናል፡፡ ነገር ግን ከአመት በፊት በዚህ መልኩ ስራው እንዲሰራ ተሞክሮ የነበረ ሲሆን መቶ በመቶ ማለት በሚቻል መልኩ ሳይሳካ ቀርቶ ወደ ነበረው አሰራር ተመልሷል፡፡
መ/ቤቱ የራሱን ሰዎች ደላላ ለማድረግ ቆርጦ የተነሳበት አሰራር በህግ ለማስደገፍ እየተሞከረ ነው
ስራው በምደባ ብቻ መሰራት አለበት ለሚለው ሀሳቡ ሚ/መ/ቤቱ የሚያቀርበው ምክንያት ዜጎች ለኤጀንሲዎች በሚያቀርቡ ደላሎች ብዝበዛ እየደረሰባቸው ነው የሚል ሲሆን ለዚህ መፍትሄው ከጎረቤት ኬንያን፣ ኡጋንዳ ከመሰሉ ሀገራት ተሞክሮ ወስዶ ከማስተካከል ይልቅ ውጭ ላይ ህገ ወጥ ያሏቸውን ደላሎች አስወጥተው መ/ቤቱ የራሱን ሰዎች ደላላ ለማድረግ ቆርጦ የተነሳበት አሰራር በህግ ለማስደገፍ እየተሞከረ ነው፡፡
ከዚህ በተጨማሪ የዋስትና ገንዘብ ከዚህ በፊት በኤጀንሲው ስም በተከፈተ ዝግ አካውንት ይቀመጥ የነበረውን በሚ/መ/ቤቱ ሂሳብ ቁጥር እንዳናስገባ እና መጠኑም በፊት ከነበረው 100000 የአሜሪካን ዶላር ወደ 200000 የአሜሪካን ዶላር እንዲያድግ መደረጉን ከተነበበልን ረቂቅ መረዳት ችለናል፡፡
በኤጀንሲው ስም በተከፈተ ዝግ የሂሳብ ቁጥር በመቀመጡ ምንም የተፈጠረ ችግር በሌለበት ሁኔታ ውስጥ እንደዚህ ለማድረግ የተፈለገበት ምክንያት ገንዘቡ እውነት ለዋስትና ነው ወይስ ለሌላ የሚል ጥርጣሬ ያችራል፡፡
ለዚህ በምክንያትነት ያስቀመጡት ኤጀንሲዎች ፎርጂድ የዋስትና ደብዳቤ እያቀረቡ ነው የሚል ሲሆን ነገር ግን ፎርጂድ እንዳይመጣ በቀላሉ የሲስተማቸውን አክሰስ ለባንኮች በመስጠት (ልክ ለሌሎች ተቋማት በመስጠት ፎርጂድን ማስቀረት እንደቻሉት) ችግሩን መፍታት ይችሉ ነበር፡፡
የዛሬ አንድ አመት አካባቢ ጠ/ሚንስትሩ አንድ ማብራሪያ በሰጡበት አንድ ቦታ ላይ ባንኮች ላይ ስለሚፈፀም ማጭበርበር በተናገሩበት ወቅት 90 በመቶ የሚሆነው ኤጀንሲ ከአንድ ባንክ ጋር ብቻ እንደሚሰራ የባንኮች የማጭበርበር ምሳሌ አድርገው ማቅረባቸውን እናስታውሳለን፡፡
ነገር ግን ኤጀንሲዎች ከባንኩ የሰሩት በማጭበርበር መልኩ ሳይሆን ብሄራዊ ባንክም ጭምር በሚፈቅደው የዋስትና አሰጣጥ ዘዴ ነው፡፡ ነገር ግን ይህን አዋጅ ለማውጣት እንዲመችና የሚመጣባቸውንም ክርክር ለመቀነስ በሚመስል መልኩ የተዛባ መረጃ ለጠ/ሚንስትሩ እንደቀረበ ለመረዳት አዋጁ እየሄደበት ያለውን መንገድ ማየት በቂ ነው፡፡
መረጃን ከመሠረት!
መሰረት ሚዲያን ለዘገባው እናመሰግናለን
የውጭ አገር ስራ ስምሪት ላይ እየተፈፀመ ያለው ብዝበዛ በተለይም በመስሪያ ቤቱ ለሲስተም ማበልፀግ ፕሮጀክት በተቀጠሩት ሰራኞች እጅግ አስገራሚና አይን ያወጣ ነገር ነው፡፡ ሲስተሙን በመጀመሪያ ደረጃ የመረጃና ደህንነት ኤጀንሲ የሚባለው ኢንሳ እራሱ የሚያውቀው አይመስልም፡፡ የዛሬ አመት አካባቢ 18000 የሚሆኑ ዜጎች እዚህ ሲስተም ላይ አድሚን በሆኑና ፕሮጀክቱን በሚመሩ ሰዎች አማካኝነት ህገወጥ የኢሚግሬሽን ማለፊያ ወይም ኪው አር መውጣቱ ኦዲት ላይ ተረጋግጦ ሳለ ሚንስትሯ በነዚህ ሰዎች ላይ ምንም እርምጃ አለመውሰዷ የጥቅም ቁርኝት እንዳላቸው ያሳብቃል፡፡ አሁን ደግሞ ይባስ ብሎ ከዚህ በፊት በመ/ቤቱ በመሪ ስራ አስፈፃሚነት ደረጃ የነበሩትን ሴት ለሲስተም ክፍሉ አልታዘዝም በማለታቸው ምክንያት ከስራቸው በማባረር፣ የሲስተም ክፍሉን ቡድን ሲመራ የነበረ ለቦታው በቂ የትምህርት ዝግጅት ቢኖረው እንኳን ቦታው የሚፈልገውን የስራ ልምድ የሌለውን ሰው ሚንስትሯ በመሾም እነሱ የሚፈልጉትን ብቻ ለማስፈፀም እየሞከሩ እንደሆነ አይተንበታል፡፡ ይህ ግለሰብ ቦታውን ከያዘ ጀምሮ በየእለቱ የተለጠፉ ማስታወቂያዎች ብዛት የመ/ቤቱም ግድግዳ የቻለው አይመስልም፡፡ አንድን ትልቅ ሴክተር ከመመሪያ ይልቅ ማስታወቂያ እየመራው ነው ብንል ይቀላል፡፡
ይህ ዘርፍ አዋጅና መመርያ ቢወጣለትም ጠያቂ በሌለው ሚ/ር መ/ቤቱ ማዘዝ እንጂ ማዳመጥ በመይወዱት ሚንስትሯ ማን እና ምን እንደሆነ በማይታወቅ አካል (ስምና ሀላፊነቱ ተጠቅሶ በማይታወቅ አካል የየቀን የግድግዳ ላይ ማስታወቅያ) የሚመራ በዚህ አካሄድም እየጠፋ ያለ ዘርፍ ነው
እኔ በዚህ ዘርፍ ላይ ከአምስት በላይ ሚኒስትሮችን አውቃለሁ ህግና ደንቡ በየሚንስትሩ ልክ ሲሻሻልም አውቃለሁ ነገር ግን በማንም የአስተዳደር ጊዜ ስምና ሀላፊነቱ በማይታወቅ አካል ፍላጎትና ስሜት ሲመራ ሳይ የመጀመርያዬ ነው
እንደሀገር ሚ/ር/መ/ቤቱ እያከናወነ ያለው ነገር ያማል ሙሉለሙሉ በሚባል ደረጃ ሚናውን ስቷል አንዴ ትኬት ካልቸረቸርኩ በሚል ሲስተሙን በመዝጋት ለበረራ የተዘጋጁ ልጆችን ሲያንከራትት ሌላ ጊዜ ልጆቹን እኔ መልምዬ ለኤጀንሲዎች ካልሰጠሁ እያለ የበረሩ ልጆችን ሳይቀር ለኤጀንሲዎች እየበተነ ከተማዉን የማያውቁ ልጆችን ሲያንከራትት ስራውን ሲያስተጓጉል ዘርፉን ለማጥፋት ቆርጦ የተነሳ እንጂ ዘርፉን ለማዘመን ያሰበ አይመስልም
ከዚህ ሁሉ በላይ ጥያቄ ያነሳ የዘርፉ ባለቤት የሚደርስበትን ስለሚያውቅ ሚ/ር/መ/ቤቱ ዘርፉን ከማዘጋቱ በፊት የቻልኩትን ያህል ልስራ በሚል ተስፋ መቁረጥ ሚ/ር/መ/ቤቱ ግድግዳ ላይ በሚለጠፍ ቁራጭ ወረቀት ቀጭን በማስፈራርያ የታጀበ ማስታወቅያ መሠረት መስመሩን ሳይስት ለመሄድ እየሞከረ ይገኛል
የሚያሳዝነው ግን የሁል ጊዜ በግፅ ኤጀንሲዎች በዝታቹዋል መቀነስ አለባቹ (100 ኤጀንሲዎች ብቻ!!! )የሚለው አይን ያወጣ በማን አለብኝነት ያሸበረቀ የሚ/ር/መ/ቤቱ ግልፅ አቋም ምንም እንኳን አዲስ ፍቃድ አቆምኩኝ ቢልም በጎን በድብቅ የሚሰጣቸው አዳዲስ ፍቃዶች መብዛትን ላስተዋለ 100ዎቹ ሚ/ር/መ/ቤቱ የሚፈልጋቸው ኤጀንሲዎች ሲሞሉ አሁን ያሉትን ሙሉ ኤጀንሲዎች በተለመደ ማንአለብኝነት እንደሚያግድ እና ከስራ ውጭ እንደሚያደርጋቸው ግልፅ ይሆንለታል።
ለዚህም ማሳያው ትላንት ያወጣው ከ100 በላይ ኤጀንሲዎችን የማገድ ስራ በቂ ማስረጃ ነው
ስለዚህ ሚ/ር/መ/ቤት አሰራር ግድፈቶች አይደለም በአስተያየት በእድሜዬ ልክ ፅፌ የማልጨርሰው በመሆኑ አዝናለሁ
ሰሚ ካለ ግን ይህ ዘርፍ ለሀገሬ በእጅጉ የሚያስፈልጋት ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች የምታገኝበት በመሆኑ አንዴ ከተዘጋ ክብርት ሚኒስትሯ (ይዘጋ እናሰማ ከፍተዋለን!) እንደሚሉት ቀላል አይሆንም ምክንያቱም በሀገር ያለን የስራ እድል ልክ እን ኤጀንሲው እንደፈለጉ መክፈትና መዝጋት ቀላል አይደለም