(መሠረት ሚድያ)- "እኔ አንድ የቅርብ ዘመድ አለኝ። የውጭ ሀገር ፕሮሰስ እጀምራለሁ ብሎ የከፈላት ሴትዮ ፕሮጀክቱን የሚመሩት ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ናቸው ብላ ከ100 መቶ ገደማ ሰዎች ከእያንዳንዳቸው ከ200 ሺህ ብር ጀምሮ እስከ 1.2 ሚልዮን ብር ተቀብላለች።"
የምርመራ ዘገባችንን ለመጀመር መነሻ የሆነን ይህ ከላይ ያቀረብነው የአንድ የመሠረት ሚድያ ተከታታይ ጥቆማ ነበር። ጥቆማችንን ይዘን የምርመራ ዘገባችንን ስናሰፋ 'ምሮን ፕሮዳክሽን'፣ አንዳንዴ ደግሞ ስሙን ቀየር አርጎ 'ማይካራህ' ወደሚባል ድርጅት ይወስደናል።
ድርጅቱ እንደሌሎች ድርጅቶች ውጭ ሀገር ለትምህርት እንልካለን፣ ስራ እናስቀጥራለን ወይም ቪዛ እናስመታለን ብሎ የሚያቆም አይደለም።
አሜሪካ እና ካናዳ ሰዎችን በቀላሉ መላክ እንደሚችል የሚገልፀው እና በአብዛኛው በቴሌግራም ላይ ብቻ የሚንቀሳቀሰው ድርጅቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ከመንግስት መስሪያ ቤቶች ጋር አብሮ እንደሚሰራ ይናገራል፣ ይህም የተጭበርባሪዎችን እምነት ለማግኘት ነበር።
"ፓስፖርት ተቀብላ ቪዛው አልቋል፣ ቅዳሜ ትሄዳላችሁ ካለች በኋላ ለሶስት ወር ጠፍታ ስትመጣ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለስራ ወደ የተለያዩ ሀገሮች ስለሄዱ እኔም አብሬ ደርሼ መጣሁ አለችን" የሚሉት አንድ የድርጊቱ ሰለባ ናቸው።
"አይ፣ በቃን ብር ይመለስልን ያሉትን ልጆች ማስፈራራት ጀመረች። የቴሌግራም ግሩፑ ላይ ከ80 ሰው በላይ ያለ ሲሆን የጠቅላይ ሚኒስቴር ቢሮ የሚልም ኮንታክት ሴቭ ተደርጎ አለበት" በማለት እንዴት እንደተታለሉ ያስረዳል (ምስሉ ተያይዟል)።
መሠረት ሚድያ ባደረገው ማጣራት የዚህ ድርጊት ፈፃሚ ማህሌት አረፈሸዋ ዘለቀ የምትባል ሲሆን የኮልፌ ወረዳ 6 ነዋሪ ነች። ለዚህ ዘገባ በሚድያችን በተደጋጋሚ ምላሽ እንድትሰጥ ብትጠየቅም ፈቃደኛ ሳትሆን ቀርታለች።
ከምሮን ፕሮጀክት ለአባላቱ የተላከ ይህን መልዕክት በቀጥታ እናቅርብ:
ለምሮን ፕሮጀክት አባላት በሙሉ፦
ሠላም ለእናንተ ይሁን!!
በጣም አስቸኳይ!!!
የአሜሪካና የካናዳ ኤምባሲዎች ቀጠሯችን ነገ መሆኑ ይታወቃል። ስለሆነም፦
- የአሜሪካን 1ኛ ዙር የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ የሆናችሁ የፕሮጀክት አባላት ብቻ ነገ ከጠዋቱ 1:00 ሰዓት ላይ ሽሮ ሜዳ ከሚገኘው የአሜሪካን ኤምባሲ ፊት ለፊት
- የካናዳ ኤምባሲ 1ኛ ዙር የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ የሆናችሁ የፕሮጀክት አባላት ብቻ ደግሞ ነገ ከቀኑ 6:00 ሠዓት ካርል አደባባይ አካባቢ ሳር ቤት፤ ከICS ት/ቤት አካበቢ በሚገኘው የካናዳ ኤምባሲ እንድትገኙ በጥብቅ እያሳሰብኩ ስንገባ ስልኮቻችን መፈተሽ ስለሚፈልጉ፦
1ኛ- ስትጠቀሙበት የነበረውን ስልክ ጥሎ መግባት አይቻልም። ይዞ መገኘት የግድ ነው።
2ኛ- በስልካችሁ ውስጥ ያሉ በ facebook፣ በ tiktok፣ whatsup ወዘተ ላይ የተጻጻፋችኋቸው የፖለቲካና እምነትን የሚያንቋሽሹ መልዕክቶች እና ሌሎችም አላስፈላጊ መልዕክቶች ቢኖሩ እንድታጠፉ (ቢቻል አፕልኬሽኖቹን ብናጠፋቸው ይመከራል።)
3ኛ- ከአሁን በፊት እንድታጠኑ የተሰጧችሁ የነገስታቱ ፎቶዎችና ሌሎች የማይክራ ፕሮጀክት መልዕክቶች ያለባቸውን የትኛቸውንም ዶክመንቶች ማጥፋት ይጠበቅባችኋል።
4ኛ- ከክፍያ ደረሰኝ፣ ፓስፖርት፣ የልደት ካርድ፣ የጋብቻ ሰርተፊኬትና መሠል ለጉዞ የሚያገለግሉ ዶክመንቶች ውጭ የትኛውንም በስልክና በቴክስት የተለዋወጥናቸውን ንግግሮችና መልዕክቶች ማጥፋት አስፈላጊ ነው።
ማሳሰቢያ: ሰዓት በማሳለፍ ለሚፈጠር ችግር ኃላፊነት የሚወስደው ራሱ ግለሰቡ ነው። የ2ኛውን ዙር ፕሮግራም ነገ የማሳውቅ ይሆናል።
እግዚአብሔር ይባርካችሁ!!!!
ማህሌት አረፈሽዋ ዘለቀ
ግለሰቧ ይህን መልዕክት ካስተላለፈች በኋላ ደግሞ ይህን መልዕክት ወዲያው አስከተለች:
የአሜሪካና የካናዳ ኤምባሲዎች ቀጠሯችን ዛሬና ነገ መሆኑ ይታወቃል። ይሁን እንጂ ወደ ኤምባሲ መግባቱ ስለቀረ ቪዛችሁን ቅዳሜ የካቲት 8/2017 ጠዋት 3:00 ሠዓት በቀጥታ መገናኛ ከሚገኘው ዲ ኤች ኤል (DHL) ማዕከል በአካል በመገኘት እንድትወስዱ አሳስባለሁ።
እግዚአብሔር ይባርካችሁ!!!!
ማህሌት አረፈሽዋ ዘለቀ
ግለሰቧ ከጠ/ሚሩ ጋር የቅርብ ግንኙነት እንዳላት፣ የቀዳማዊ እመቤት ዝናሽ ታያቸው ጓደኛ እንደሆነች እና የኖቤል ሽልማት ወቅት ተገኝታ እንደነበር የሚያሳይ ፎቶ እንዳሳየቻቸው ተጭበርባሪ ግለሰቦቹ ለሚድያችን ተናግረዋል።
"ገንዘቡን የሰበሰበችው በሁለት መልኩ ነው፣ አንደኛው ሙሉ ክፍያ መክፈል ከሚችሉት 1.2 ሚልዮን ብር ወሰደች። ብር የለንም ካሉት ደግሞ 500 ሺህ ብር ወስዳ ቀሪውን 700 ሺህ ብር ወደ አሜሪካ እና ካናዳ ከሄዱ በኋላ እንዲከፍሉ በማስማማት ነበር። ብዙዎቹን ቸርች አካባቢ አግኝታ ያጠመደቻቸው ናቸው" በማለት ሌላኛው ተጎጂ ይናገራሉ።
አክለውም "ጉዳዩን የጠ/ሚር ቢሮ ይዞታል፣ አሁን ለግዜው ያዝ ስላረጉት ነው። ያለቀ ጉዳይ ነው፣ ተረጋግታችሁ ጠብቁ እንባላለን። ልጆቻቸውን ከትምህርት ቤት አስወጥተው ወደ ውጭ ለመሄድ ለበረራ እየተዘጋጁ ያሉ ሰዎች ነበሩ። በርካታ ቤተሰቦች በዚህ መልኩ ተጎድተው ይገኛል" በማለት ሁኔታውን ያስረዳሉ።
የወንጀሉ ሰለባዎች 'ይህን ነገር እውነት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ያውቁታል ወይ? ነው ወይስ በጠቅላይ ሚኒስትሩ ስም ንግድ ጀምረው ነው?' የሚል ጥያቄ መጠየቅ የጀመሩት ከረፈደ በኋላ ቪዛቸውን ማግኘት ሳይችሉ ሲቀሩ ነበር።
ይሁንና ለምን ብለው የሚጠይቁ እና ብር ይመለስልን ለሚሉ በተለያዩ ሰዎች በማስደወል እንደምታስፈራራ እና አልፎ አልፎ ቴሌግራም ላይ ማስፈራርያ አዘል መልዕክት እንደምታስቀምጥ ተመልክተናል። አንዱን የግለሰቧን መልዕክት ያድምጡ:
ከሁሉም አስገራሚው ድርጊት ደግሞ ተበዳዮቹ ባለፉት ጥቂት ቀናት ተሰባስበው ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንውሰድ ብለው የደረሰባቸው ነገር ነበር።
"ግለሰቧ ይህን ስትሰማ በመሀል የቴሌግራም ግሩፑ ላይ ገብታ አለሁ በማለት እንግሊዝ ኤምባሲ ፊት ለፊት የሚገኘው አሜን ቁርጥ ቤት ቀጠረች። ሁሉም የሴትዮዋን መምጣት ሲጠባበቅ እሷ ግን የፌደራል ፖሊስ አባላትን በመላክ አስደንብራ እና አስፈራርታ በተነች" በማለት የሆነው አስረድተዋል።
በዚህ ሁኔታ የተጭበረበሩ ሰዎች ቢያንስ ከዘጠና እስከ አንድ መቶ እንደሚሆኑና በግምት 80 ሚልዮን ብር ገደማ እንደተጭበረበሩ ታውቋል።
"ይህ ሁሉ ሲሆን መንግስት አያስቆማትም ወይ? በጠቅላይ ሚኒስትሩ እና በቢሯቸው ስም ስትነድግ ይባስ ብሎ ፖሊሶችን እየተጠቀመች እንድንፈራ ይደረጋል፣ ይህ እጅግ አሳዛኝ ነው፣ መፍትሄ ይሰጠን" በማለት መልዕክታቸውን አቅርበዋል።
ግለሰቧ በአሁን ሰአት ሁሉም መገኛዋን አጠፋፍታ ያለችበት ቦታ እና ሁኔታ እንደማይታወቅ እነዚህ የድርጊቱ ሰለባዎች ጠቁመዋል።
መሠረት ሚድያ በቅርቡ በተመሳሳይ የማጭበርበር ድርጊት ላይ ተሰማርታ የምትገኝ እና 'ቤተልሄም ታደሰ ይማም' ስለምትባል ግለሰብ መረጃ ማቅረቡ ይታወሳል። የሚድያችን ተከታታዮች ከእንዲህ አይነት የማጭበርበር ድርጊት ራሳቸውን እንዲጠብቁ እንመክራለን።
መረጃን ከመሠረት!
እራሱን ለአጭበርባሪዎች በዚህ ልክ ተጋላጭ የሚያደርግ ግለሰብ/ስብስብ ካለ፣በአቋራጭ (በልዩ ትስስር) ለመበልጸግ/የማይገባውን ጥቅም ለማግኘት የሚከጅል ስግብግብ ነው።ስለዚህም ደግ አደረገቻቸው።(አልጠግብ ባይ ሲተፋ ያድራል ነው ነገሩ) That is how i feel.
በጣም የሚገርምመው ሴትዮዋ እንደ ቋሚ አድራሻ ስትጠቀምባቸው የነበሩ የኪራይ አፓርትመንቶች ውስጥ እንደነዋሪ እንድትታይ ህፃናት ልጆችን ጭምር ስታሳትፍ የነበረ ሲሆን በተግባር ግን በየ15 ቀኑ ቦታ ትቀያያይር የነበር መሆኑ ነው!